
መቀመጫውን እስራኤል አገር ያደረገውና ጄዊሽ ቮይስ ሚኒስትሪስ በመባል የሚታወቀው ክርስቲያናዊ የተራዶ ድርጅት፣ በኮንሶ ዞን ካራት ከተማ ነጻ የህክምና አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ከአካባቢው የወጡ መረጃዎች አመለከቱ።
የድርጅቱ ከፍተኛ የህክምና ቡድን ቅዳሜ ህዳር 24 ቀን 2015 ዓ.ም ወደ ካራት ከተማ በገቡበት ወቅት የዞንና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት ደማቅ አቀባበል እንደተደረገላቸው፣ የዞን መንግሥት ኮሚዩኒኬሽን አስታውቋል።አቀባበል ከተደረገላቸው በኋላ አንዳንድ ታሪካዊ ቦታዎችንም ጎብኝተዋል።
ከትላንት እሑድ ህዳር 25 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ ለ5 ተከታታይ ቀናት በካራት ጤና ጣቢያ ህክምናውን እየሰጡ እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን፣ ቢያንስ 10 ሺህ ያህል ታካሚዎች የአገልግሎታቸው ተጠቃሚ ይሆናሉ ተብሎ ይጠበቃል።

በአምስቱ ቀናት የሚከናወነውን ነጻ የህክምና አገልግሎት ለመስጠት ለመድኃኒቶች፣ ለህክምና መገልጊያ ቁሳቁሶችና ለሌሎች አስፈላጊ መሣሪያዎች በተቋሙ በኩል ከ18 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉም ተገልጿል።
ድርጅቱ ከዚህ ቀደም ከመስከረም 8-15 ቀን 2015 ዓ.ም በጌዴኦ ዞን ተመሳሳይ ነጻ የህክምና አገልግሎት መስጠቱ በወቅቱ በደቡብ ራድዮና ቴሌቪዥን ድርጅት መዘገቡ ይታወሳል።

ጄዊሽ ቮይስ ሚኒስትሪስ መቀመጫውን በእስራኤል አገር ያደረገ ክርስቲያናዊ ምግባረ ሰናይ ተቋም ሲሆን፣በዓለም ዙሪያ አይሁዶች ባሉባቸው አገሮች በተለይ ለአይሁዶች ወንጌልን ማሠራጨትና ከዚሁ ጎን ለጎን የበጎ አድራጎት ተግባራትን በመፈጸም የሚታወቅ የተራዶ ድርጅት ነው።