በኮንሶ ዞን የሰገን ዙሪያ ወረዳ ከጸጥታ ችግሮች ነጻ እንዲሆን የዞኑ መንግሥት በትኩረት እየሠራ መሆኑ ተገለጸ

በኮንሶ ዞን የሰገን ዙሪያ ወረዳ ከጸጥታ ችግሮች ነጻ እንዲሆን የዞኑ መንግሥት በትኩረት እየሠራ መሆኑ ተገለጸ

በኮንሶ ዞን ሰገን ዙሪያ ወረዳ የጸጥታ ሥጋቶች ተቀርፈው ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን፣ ከአጎራባችን ልዩ ወረዳዎች ጋር በትኩረት እየሠራ መሆኑን፣ የዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ገበየሁ አስታወቁ።

አስተዳዳሪው ይህንን የተናገሩት በገና ዋዜማ ወረዳውን በጎበኙበትና በወቅታዊ አካባቢያዊ ጉዳዮችና በመጪው “የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል” ህዝበ ውሳኔ ዙሪያ ከወረዳው አመራርና ነዋሪዎች ጋር ውይይት ባደረጉበት ወቅት ነው።

የሰገን ዙሪያ ወረዳ፣ አከባቢው ላይ በመሸጉና ከአጎራባችን የዲራሼ ልዩ ወረዳ በሚነሱ ጸረ ሰላም ኃይሎች ተደጋጋሚ ጥቃቶች ሲፈጸሙበት የቆየ አካባቢ መሆኑ ይታወቃል። ይሁንና በተደጋጋሚ በተደረጉ ህግ የማስከበር ተግባራትና በቅርቡም ከአጎራባች የዲራሼ ልዩ ወረዳ ህዝብና አመራር ጋር የሰላም ኮንፍራንሶች መደረጋቸውን ተከትሎ፣ የአከባቢው ሰላም እየተመለሰ ይገኛል።

የውይይቱ ተሳታፊዎች

ዋና አስተዳዳሪው ከሰገን ዙሪያ ወረዳ ማህበረሰብ ጋር ውይይት ባደረጉበት ወቅት፣ በቀደሙት ግጭቶች ወቅት ከቀዬያቸው ተፈናቅለው እስከ አሁንም ድረስ ወደ መኖሪያቸው ያልተመለሱና ድጋፍ የሚሹ ወገኖች ስለመኖራቸው የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ በርሻ ኦላታ አስታውቀዋል።

በውይይቱ የተሳተፉ የወረዳው ነዋሪዎች፣ ባለፉት ጊዜያት ባለማወቅ የጠፉ ጥፋቶች ከእንግዲህ እንዳለፉ በማሰብና ይቅር በመባባል፣ አሁን የተገኘውን ሰላም በማስቀጠል ረገድ የበኩላቸውን ሚና እንደሚጫወቱ ቃል ገብተዋል።

በዚህ ሁሉ ችግርና ግጭቶች መሃል የአብሮነት እሴቶችን በማጉላት፣ ግጭቶችን ለማስቆምና ዘላቂ ሰላም በቀጠናው እንዲሰፍን ከፍተኛ ሚና ለተጫወቱ ግለሰቦች የምሥጋና የምስክር ወረቀት መበርከቱን፣ የዞን መንግሥት ኮሚዩኒኬሽን መስሪያ ቤት አስታውቋል።

በተመሳሳይ ዜና፣ በሰገን ዙሪያ ወረዳ ቀበሌያትና በአጎራባች የዲራሼ ልዩ ወረዳ ቀበሌያት መካከል በየጊዜው የሚከሰቱ የጸጥታ ችግሮችን ለመቅረፍ የወረዳው አመራር ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት ማድረጉን፣ የሰገን ዙሪያ ወረዳ ኮሚዩኒኬሽን መሥሪያ ቤት አስታውቋል።

በሰገን ዙሪያ ወረዳ ጋርጬና አይሎታ ዶካቱ ቀበሌያትና በአዋሳኝ የዲራሼ ልዩ ወረዳ ቀበሌያት መካከል አሁንም አልፎ አልፎ ትንኮሳዎች መኖራቸው የተገለጸ ሲሆን፣ ይህም ሰላምን የማይፈልጉና ጫካ ሸፍተው በየጊዜው ከብቶችን የሚዘርፉና አልፎ አልፎም በሰው ህይወት ላይ ጉዳት የሚያደርሱ አካላት በመኖራቸው ነው ተብሏል።

በውይይቱ ወቅት፣ ከአጎራባች የዲራሼ ልዩ ወረዳ ህዝብ ጋር ከሚደረጉ የሰላም ውይይቶች በተጨማሪ በነዚህ ሽፍቶች ላይ የሚወሰደው ህጋዊ እርምጃ መቀጠል እንዳለበት፣ ከውይይቱ ተሳታፊዎች መነሳቱ በኮሚዩኒኬሽን መሥሪያ ቤቱ ዘገባ ተገልጿል።

Comments

No comments yet. Why don’t you start the discussion?

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *