
በኮንሶ ዞን ከተለያዩ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተመርቀው ሥራ ላላገኙ ወጣቶች ሥልጠና መሰጠቱን፣ የዞን የመንግሥት ኮሚዩኒኬሽን መሥሪያ ቤት አስታውቋል። ሥልጠናው የተሰጠው በደቡብ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ፣ በደቡብ ክልል አመራር አካዳሚና በኮንሶ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ የጋራ ቅንጅት መሆኑ ተገልጿል።
ሥልጠናው ሰልጣኞች የሥራ ፈጠራ ክህሎት እንዲያዳብሩና የሥራ ፍላጎታቸውና ተነሳሽነታቸው እንዲጨምር ለማድረግ ያለመ ነው ተብሏል።
ወጣቶችንና ሥራን የሚመለከቱ ብሔራዊ ፖሊሲዎች፣ የህይወት ክህሎቶች፣ ሥራ ፈጠራና የቢዝነስ ዕቅድ አዘገጃጀት፣ በሥልጠናው ትኩረት የተሰጠባቸው ርዕሰ ጉዳዮች ናቸው።

የሥልጠናው ተሳታፊዎች፣ ስልጠናው ከፍተኛ መነሳሳትን በውስጣቸው እንደፈጠረ ገልጸው፣ ተደራጅተው የራሳቸውን ሥራ በመፍጠር ከሥራ ጠባቂነት ወደ ሥራ ፈጣሪነት ለመሸጋገር የሞራል ስንቅ እንዳገኙበት መናገራቸው ተመልክቷል።

በሥልጠናው ላይ የተገኙት የካራት ከተማ ከንቲባ አቶ ፍሬዘር ኮርባይዶም፣ ወጣቶች በሥልጠናው ያገኙትን ክህሎት ወደ ተግባር ለመለወጥ በሚያደርጉት ጥረት በኢንተርፕራይዞች ሴክተር በኩል አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ገልጸው፣ ሰልጣኞችም የቀሰሙትን ዕውቀት ወደ ተግባር ለመለወጥ ጥረት እንዲያደርጉ አሳስበዋል።